Psalms 57

በጨካኝ ጠላቶች ዘንድ

57፥7-11 ተጓ ምብ – መዝ 108፥1-5

ለመዘምራን አለቃ፤ “አታጥፋ” በሚለው ቅኝት የሚዘመር፤ ከሳኦል ፊት ሸሽቶ በዋሻ በነበረበት ጊዜ፤ የዳዊት ቅኔ
ርእሱ የሥነ ጽሑፉን ቅርጽ ወይም የመዝሙሩን ሁኔታ የሚያሳይ ሊሆን ይችላል።

1ማረኝ፤ እግዚአብሔር ሆይ፤ ማረኝ፤
ነፍሴ አንተን መጠጊያ አድርጋለችና፤
በክንፎችህ ሥር እጠለላለሁ።

2ለእኔ ያሰበውን ወደሚፈጽምልኝ አምላክ፣
ወደ ልዑል እግዚአብሔር እጮኻለሁ።
3ከሰማይ ልኮ ያድነኛል፤
የረገጡኝን ያዋርዳቸዋል፤ ሴላ
እግዚአብሔር ምሕረቱንና ታማኝነቱን ይልካል።

4ነፍሴ በአንበሶች ተከብባለች፤
በሚዘነጣጥሉ አራዊት መካከል ወድቄአለሁ፤
እነዚህም፣ ጥርሳቸው ጦርና ፍላጻ፣
ምላሳቸውም የተሳለ ሰይፍ የሆኑ ሰዎች ናቸው።

5እግዚአብሔር ሆይ፤ ከሰማያት በላይ ከፍ ከፍ በል፤
ክብርህም በምድር ሁሉ ላይ ትስፈን።

6ለእግሬ ወጥመድን ዘረጉ፤
ነፍሴንም አጐበጧት፤
በመተላለፊያዬ ላይ ጕድጓድ ቈፈሩ፤
ነገር ግን ራሳቸው ገቡበት። ሴላ

7እግዚአብሔር ሆይ፤ ልቤ ጽኑ ነው፤
ልቤ ጽኑ ነው፤
እቀኛለሁ፤ አዜማለሁ።
8ነፍሴ ሆይ፤ ንቂ!
በገናና መሰንቆም ተነሡ
እኔም በማለዳ እነሣለሁ።

9ጌታ ሆይ፤ በሕዝቦች መካከል አመሰግንሃለሁ፤
በሰዎችም መካከል እዘምርልሃለሁ፤
10ምሕረትህ እስከ ሰማያት ከፍ ብላለችና፤
ታማኝነትህም እስከ ደመናት ትደርሳለች።

11እግዚአብሔር ሆይ፤ ከሰማያት በላይ ከፍ ከፍ በል፤
ክብርህም በምድር ሁሉ ላይ ትስፈን።
Copyright information for AmhNASV